"በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረች ስትሆን መልሳ አምላኳን በሥጋ በመልኳ እና በምሳሌዋ ስለ ወለደችው ድንግል፣ ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ ላለው የዓለም እረኛ ቀድማ የድንግልናዋን ወተት ስላጠጣችው እመቤት፣ የጽድቅ ፀሐይ ክርስቶስ ስለ ወጣባት የምሥራቅ ደጅ፣ የብርሃናት አባት ስለ ፈነጠቀባት ብርህት አዘቅት ምን እንላለን? አንደበት ሁሉ በገናንነቷ ፊት ዲዳ ይሆናል፡፡ ቀለም ይነጥፋል፤ ብዕርም ይዶለዱማል፡፡ ባሕር ሊቀዝፍ ገብቶ እንደ ዛለ የዋናተኛ ክንድ ኅሊና ይደክማል፡፡ ነገር ግን ለስም አጠራሯ ምስጋና ይግባትና ስለ እርሷ በመናገር የሚገኘው በረከት እንዳይቀርብን ከበዛው እና መጠኑ ከማይታወቀው ምሥጋናዋ ጥቂት ጥቂት የሚነግሩን የታደሉ ምስክሮችን ደግሞ ትሰጠናለች፡፡ ከእነዚህም አንዱ 'የብርሃን እናት' እነሆ "
ዲያቆን አቤል ካሣሁን (ሰባኬ ወንጌልና ደራሲ) ስለመጽሐፉ ከሰጠው አስተያየት የተወሰደ